መንግሥት “የአረንጓዴ አሻራ” በሚል ፕሮግራም በአንድ ቀን 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ዘመቻ ዛሬ አካሂዳለች።
በዚህ ችግኝ የመትከል ዘመቻ “805 ነጥብ 3 ሚሊዮን” ችግኞችን በመትከል ታላቁን ሀገራዊ እቅድ በላቀ ስኬት ማጠናቀቋን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አሳውቀዋል።
በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ተሳትፈውበታል በተባለው በዚህ መርሃ ግብር ሀገሪቱ በአንድ ቀን ከዚህ በፊት ተይዞ የነበረውን የ700 ሚሊዮን ችግኝ መትከል ሪከርድን እንዳሻሻለች ተገልጿል።
የመንግሥት ኮሙንኬሽን ባወጣው መግለጫ በኢትዮጵያ የተራቆቱ አካባቢዎች በልጆቿ ብርቱ እጆች እንዲታከሙ፣ እየተስፋፋ የመጣው ድርቅና በረሃማነት በዘላቂነት እንዲገታ እና በአስተማማኝ መሠረት ላይ የተገነባ አረንጓዴ ኢኮኖሚ እውን እንዲሆን ግልጽና ጽኑ አቋም መያዙን ገልጿል።
ባለፉት ሰባት ዓመታት ብቻ በአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን የገለጸው ተቋሙ ዘንድሮም በንቅናቄው 8ኛው ዓመት በአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን፣ በክረምቱ ደግሞ በአጠቃላይ 8 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል መንግሥት ቁርጠኛ አቋሙን በይፋ አሳውቋልም ብሏል።
በዚህም በዛሬው ዕለት 26 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን በአንድ ጀምበር ከ805 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞችን በመትከል የተቀመጠውን ግብ ከዕቅድ በላይ መሳካቱን ገልጾ የዘንድሮው ክረምት ከገባ ጀምሮ 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኞች ተተክለዋል ተብሏል።
ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት በአንድ ቀን 718 ሚሊዮን ችግኞችን እንደተከለች የግብርና ሚንስቴር ገልጾ ነበር።