ኢትዮጵያ በሶስት ወራት ውስጥ ከወጪ ንግድ 2 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷ ተገለጸ

የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚንስቴር እንደገለጸው ባለፉት ሦስት ወራት ለውጭ ገበያ ካቀረበቻቸው ምርቶች 2 ነጥብ 48 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን አስታውቋል።

ሚንስቴሩ በበጀት ዓመቱ ሩብ ወራት ጥራጥሬንና የቅባት እህሎችን ከመሳሰሉ ምርቶች 149 ሚሊዮን ዶላር መገኘቱን ገልጿል።

በተያዘው በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ ዘርፉ ለማግኘት የታቀደው አጠቃላይ ገቢ 9 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን፣ ይህም ባለፈው በጀት ዓመት ከተገኘው ገቢ የ1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ብልጫ አለው።

ከፍተኛ ገቢ ካስገኙ ምርቶች መካከል ቡና ሲሆን 762 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷ ተገልጿል።

ገቢው የተገኘው፣ 113 ሺህ 542 ቶን ቡና በመላክ ነው የተባለ ሲሆን ከ151 ሺሕ 969 ቶን በላይ ቡና በመላክ፣ 622 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዶ እንደነበር ተገልጿል።

የኢትዮጵያን ቡና በመግዛት በቀዳሚነት የተቀመጠችው ጀርመም ስትኾን፣ ሳዑዲ ዓረቢያና ቤልጂዬም ሁለተኛና ሦስተኛ ደረጃን ይዘዋል።

ቡና፣ ማዕድናት፣ ጥራጥሬዎች፣ የኤሌክትሪክ ሀይል፣ ስጋ እና ጨርቃ ጨርቅ ምርቶች ወደውጭ ከሚላኩ ምርቶች መካከል ዋነኞቹ ናቸው።

ኢትዮጵያ ከወጪ ንግድ ከምታገኘው አጠቃላይ ገቢ ውስጥ ቡና የ35 በመቶ ድርሻ አለው።

ሀገሪቱ የወጪ ንግዷን ለማሳደግ የተለያዩ ጥረቶችን በማድረግ ላይ ስትሆን ለአብነትም ተጨማሪ የንግድ መዳረሻ ሀገራትን መፈለግ፣ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል መሆን፣ የሬሚታንስ ገቢን ማሳደግ የሚያስችሉ ስምምነቶችን እና ጥረቶችን በማድረግ ላይ ትገኛለች።

ኢትዮጵያ ከሬሚታንስ ገቢ እስከ 35 ቢሊዮን ዶላር ገቢ የማግኘት እቅም ያላት ቢሆንም እየተገኘ ያለው ግን 7 ቢሊዮን ዶላር ብቻ መሆኑን ብሔራዊ ባንክ አስታውቋል።

ለአብነትም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቤ ሳኖ ብዙ ኢትዮጵያዊያን በሚኖሩባቸው ሀገራት ደቡብ አፍሪካ፣ የተባበሩት አረብ ኢምሬት እና ሳውዲ አረቢያ በመጓዝ ከዲያስፖራ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ጋር ተወያይተዋል።

ኢትዮጵያዊያኑ ገንዘባቸውን በህጋዊ መንገድ እንዲልኩ ማግባባት እና ለዚያ የሚያበቁ ስምምነቶችን ደግሞ ከሚኖሩባቸው ሀገራት ጋር ስምምነቶችን ተደርገዋል።

By New admin

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *