ከፌዴራልና ከክልል በአጠቃላይ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሪል እስቴት ልማት ዘርፍ ለመሳተፍ ፈቃድ የወሰዱና የተመዘገቡ 6 ሺሕ የሚሆኑ አልሚዎች ያሉ ቢሆኑም፤ በሥራ ላይ የሚገኙት ግን ከ400 እንደማይበልጡ የኢትዮጵያ ሪል እስቴት አልሚዎች ማህበር አስታውቋል።
የሪል እስቴት ዘርፉ ከአልሚዎች፣ ከገዢዎችና ከፋይናንስ ተቋማት ጨምሮ፤ በርካታ ችግሮች እና ተነሳሽነት ያልነበረበት እንደነበር የገለጹት፤ የማህበሩ ም/ፕሬዝዳንት ኢንጂነር ጀበል ጀማል ናቸው።
ያለውን ችግር ለማስተካከልና በዘርፉ መተጋገዝ ካለና በጋራ መስራት ከተቻለ፤ የተሻለ ለውጥ ሊመጣ እንደሚችል በማመን የሪል እስቴት አልሚዎች ማሕበር መመስረት መቻሉንም አንስተዋል።
ማሕበሩ ከመንግሥትና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን በ29 አባላት መመስረት እንደቻለ አስታውሰው፤ አሁን ላይ ከ100 በላይ አባልትን በውስጡ መያዙን ገልጸዋል።
አሁን ላይ እንደሀገር ከተመዘገቡት 6 ሺሕ የሚሆኑ ቤት አልሚዎች መካከል ከ400 የማይበልጡት ብቻ በሥራ ላይ እንደሚገኙ ምክትል ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።
፤”እነዚህ 400ዎቹ ግን ምቹ መደላደል ተፈጥሮላቸው በጥሩ ተነሳሽነት የሚሰሩ ከሆነ ለሀገሪቱ ከበቂ በላይ ሥራን መስራት ይችላሉ” ሲሉም አክለዋል።
የቤት አልሚዎች ማሕበር ከተመሰረተ ገና 5 ወሩ እንደሆነ ገልጸው፤ ሚያዚያ 15 2017 ዓ.ም ተመስርቶ ሰኔ 7 ጠቅላላ ጉባኤ ማካሄዱን አስታውሰዋል።
ነገር ግን በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በመሆን ለማህበረሰቡ ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን ማከናወንኑን ተናግረዋል።
ዘርፉ ላይ የተሰማሩ ባለሙያዎችም ከሥራ ብቃታቸው ባሻገር በሥነ-ምግባር የታነጹ እንዲሆኑ ለማድረግ እየተሰራበት እንደሚገኝም አስታውቀዋል።
ማህበሩ ከመደበኛ ሥራው ጎን ለጎን ለሕብረተሰቡ የሚጠቅሙ የማህበራዊ አገልግሎት ላይ ንቁ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ም/ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።
አክለውም የሪል እስቴት ዘርፉን ለማሳደግና ያሉትን ክፍተቶች ለመሙላት በጋራ መስራት እንዲቻል ጥሪ አስተላልፈዋል።