የመንግሥት አጠቃላይ የአገር ውስጥ የብድር እዳ ክምችት 2.5 ትሪሊዮን ብር ደረሰ

የመንግሥት አጠቃላይ የአገር ውስጥ የብድር ክምችት 2.5 ትሪሊዮን ብር መድረሱን፣ ከዚህም ውስጥ የግምጃ ቤት ቦንድ ግዥ ከፍተኛ ድርሻ ይይዛል ተብሏል፡፡

የገንዘብ ሚኒስቴር በዕዳ አስተዳደር ክፍል በኩል ያዘጋጀውን ወርኃዊ የዕዳ ማስታወቂያ የነሐሴ ወር 2017 ዓ.ም. ሪፖርት፣ የመንግሥት አገራዊ ብድር ዝርዝር መረጃ ይፋ አድርጓል፡፡

በዚህም መንግሥት እ.ኤ.አ. ከጁን 30 ቀን 2025 ጀምሮ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ብድር 2.5 ትሪሊዮን ብር መድረሱን እንዳስታወቀ የሪፖርተር ዘገባ ያሳያል፡፡

ከአገር ውስጥ ብድር ድርሻ 80 በመቶ የሚይዘው በረዥም ጊዜ የሚከፈል የግምጃ ቤት ሰነድ እ.ኤ.አ. በኦገስት 2025 የግምጃ ቤት ሰነድ ግዥ ከፍተኛ እንደነበርና ከአጠቃላይ ክምችት አንፃርም 39 በመቶ እንደሚሸፍን ገልጿል፡፡

እስከ ኦገስት 2025 ድረስ ባለው የመንግሥት አጠቃላይ የአገር ውስጥ ዕዳ ክምችት ውስጥ ትልቁ ድርሻ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የተገኘ ብድር ሲሆን፣ ይህም 44 በመቶ ሲሸፍን፣ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የወሰደው ደግሞ ከአጠቃላይ የዕዳ ክምችቱ 27 በመቶውን ይሸፍናል። ቀሪው 18 በመቶ ደግሞ ከጡረታ ፈንድ የተገኘ ነው።

በተመሳሳይ ንግድ ባንክ 45.3 በመቶ የግምጃ ቤት ሰነዶች ባለቤትነት ድርሻ ሲኖረው፣ የጡረታ ፈንድ 32.5 በመቶ፣ ሌሎች የንግድ ባንኮች 13.5 በመቶ፣ እንዲሁም የኢንሹራንስ ኩባንያዎች 6.1 በመቶ ድርሻ መያዛቸው ተመላክቷል፡፡

በተጨማሪ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ 2.6 በመቶ ድርሻ መያዙ ተገልጿል፡፡

እ.አ.አ. በ2025/26 በጀት ዓመት የመጀመሪያዎቹ ሁለት ወራት መንግሥት በአራት የግምጃ ቤት ሽያጭ ጨረታዎች 111 ቢሊዮን ብር መሰብሰቡ በሪፖርቱ ላይ ተገልጿል።

እንደ ዘገባው ከሆነ ከተገኘው 111.1 ቢሊዮን ብር ውስጥ 78.2 በሊዮን ብር የመክፈያ ጊዜያቸው ለደረሰ የግምጃ ቤት ሰነዶች ክፍያ የዋለ መሆኑን፣ ዘጠኝ ቢሊዮን ብር ከዚህ ቀደም ሲከንባለል ለመጣ የግምጃ ቤት ሰነድ ክፍያ ውሏል ተብሏል።

እንዲሁም 23.9 ቢሊዮን ብር ደግሞ ጥቅም ላይ ያልዋለ ወይም በመንግሥት እጅ የሚገኝ እንደሆነም ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚክስ ማህበር ከሶስት ወራት በፊት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ አፈጻጸምን አስመልክቶ ባወጣው ሪፖርት ላይ እንደገለጸው ኢትዮጵያ እስከ 2023 ድረስ ያለባት የብድር መጠን 62.5 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንና የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዜጋም 575.6 ዶላር እዳ እንዳለባቸው መግለጹ ይታወሳል፡፡

By New admin

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *