የካፒታል ገበያ ባለስልጣን በጋራ ኢንቨስትመንት ፈንዶች ላይ አዲስ መመሪያ አወጣ

በአሁኑ ወቅት በካፒታል ገበያ ሥር በተለያዩ ዘርፎች አገልግሎት ለመስጠት 10 ተቋማት የፈቃድ ማመልከቻ አስገብተው እየተጠባበቁ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን አስታውቋል።

በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የምዝገባና ፈቃድ አሰጣጥ ኃላፊ አቶ እንድሪስ ሰልማን፤ በኢትዮጵያ ያለው የካፒታል ገበያ ገና በማደግ ላይ የሚገኝ መሆኑን ገልጸዋል።

ሆኖም ከጊዜ ወደጊዜ ፍላጎቱ እየጨመረ እንደሚመጣ ገልጸው፤ ያንን ፍላጎት ለመሙላት የሚያስችል ተጨማሪ አገልግሎት ሰጪዎች ገበያውን ሊቀላቀሉ የሚችሉበት ዕድል እንዳለ ተናግረዋል።

በዚህም ወደ 10 ተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ደረጃ ደግሞ አንድ ሰው የኢንቨስትመንትና የሰነደ መዋዕለ ነዋይ አማካሪነትን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የፈቃድ ማመልከቻ በማስገባት እየተጠባበቁ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።

ያመለከተው አካል በሙሉ ፈቃድ ይሰጠዋል ማለት እንዳልሆነ የገለጹት ኃላፊው፤ “በተቀመጠው የፈቃድ አሰጣጥ መመሪያ መስፈርት መሰረት አሟልተው ለሚገኙ አመልካቶች ብቻ ፈቃድ ይሰጣል” ብለዋል።

ባለስልጣን መስሪያ ቤቱም ማመልከቻቸውን በመቀበል ግምገማ እያደረገበት እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

ከዚህ ሌላ ግን እስካሁን ባለው ሂደት ፈቃድ በመውሰድ እየሰሩ የሚገኙ 8 አገልግሎት ሰጪዎች መኖራቸውን አንስተዋል።

ከእነዚህም ውስጥ 2 የኢንቨስትመንት ባንኮች ሲሆኑ፤ 5ቱ ደግሞ የሰነደ መዋዕለ ንዋይና ኢንቨስትመንት አማካሪዎች እንዲሁም አንድ የሰነደ መዋዕለ ነዋይ ገቢ አከናዋኝ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ከዚሁ ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን በሀገሪቱ የካፒታል ገበያ ላይ ያለውን የባለሀብቶች እምነት ለማሳደግ እና የክትትል ስርዓቱን ለማጠናከር የሚያስችል አዲስ መመሪያ ማውጣቱን አስታውቋል።

መመሪያው በጋራ ኢንቨስትመንት ፈንዶች ላይ ትኩረት ያደርጋል የተባለ ሲሆን፤ በተለይም እንደ ገንዘብ ገበያ፣ የጋራ ፈንዶች እና የሪል እስቴት ኢንቨስትመንት ፈንዶች ያሉ የፋይናንስ መሣሪያዎች ላይ ያለውን ግልጽነትና የቁጥጥር ደረጃ ለማሻሻል ያለመ መሆኑ ተመላክቷል።

በዚህም መሠረት መመሪያው የፈንድ አሰራሮችን ግልጽ የሆኑ ሕጎችን የሚያስቀምጥ ሲሆን፤ ባለሀብቶችን ለመጠበቅና የገበያውን ታማኝነት ለማጎልበት ዝርዝር የመረጃ ይፋ የማድረግ መስፈርቶችን ያካተተ ስለመሆኑ ባለስልጣኑ አስታውቋል።

By New admin

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *