በፌደራል ማረሚያ ቤቶች ለሚገኙ ታራሚዎች በቀን ለአንድ ታራሚ የሚመደበው በጀት 35 ብር ብቻ በመሆኑ በቂ ምግብ እያገኙ እንዳልሆነ ተገልጿል፡፡
የተመደበው በጀት አነስተኛ መሆኑ እና የወቅታዊ የገበያ ዋጋ መጨመር ጋር ተያይዞ ለታራሚዎች የሚቀርብ ምግብ በቂ እንዳይሆን አድርጎታል ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ፤ በቃሊቲ ከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ ማእከል (በተለምዶ አባ ሳሙኤል) በመባል በሚጠራው ማረሚያ ቤት የካቲት 11 ቀን 2017 ዓ.ም ጉብኝት ማድረጉን ተናግሯል፡፡
በዚህም ከምግብ አቅርቦት ማነስ በተጨማሪ አልፎ አልፎ አጃቢ የለም በማለት በቀጠሯቸው ፍርድ ቤት እና ሆስፒታል የማይወሰዱ ታራሚዎች እንዳሉም ባደረኩት ምልከታ ለማወቅ ችያለሁ ብሏል ኢሰመኮ፡፡
የአጃቢዎች እጥረት የሚፈጠረውም በማረሚያ ቤቱ የሰው ኃይል ቁጥር ማነስ እና የመርኃ ግብር መደራረብ ምክንያት እንደሆነ ተናግሯል፡፡
በማረሚያ ቤቱ የንጹሕ ውሃ አቅርቦት አነስተኛ መሆን ሌላው የማረሚያ ቤቱ ችግር ነው ብሏል፡፡
በዚህም ታራሚዎች የራሳቸውንም ሆነ የማረሚያ ቤቱን ንጽሕና ለመጠበቅ መቸገራቸውን ጠቁሟል።
የምግብ እና የውሃ አቅርቦት ችግር፤ አስቸኳይ መፍትሔ ሊሰጣቸው ከሚገቡ ጉዳዮች መካከል ዋነኞቹ ናቸው ብሏል ኢሰመኮ።
በማረሚያ ቤቱ ከታራሚዎች ቁጥር አንጻር በቂ ማረፊያ ክፍሎች፣ አልጋ እና ፍራሽ፣ መጸዳጃ እና መታጠቢያ ክፍሎች፣ የተሟላ ማብሰያ ክፍሎች እና ታራሚዎች የሚንቀሳቀሱበት ሰፊ ስፍራ እንዳለሁ ተመልክቻለሁ ሲልም ተናግሯል።
የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል የኑስ ሙሉ የማረሚያ ቤቱ መሠረተ ልማት ታራሚዎች የተነሳው የውሃ አቅርቦት ችግርን ለመፍታት ከፌዴራል ውሃ ሥራዎች ድርጀት ጋር የሥራ ውል የተገባ እና የከርሰ ምድር ውሃ ለማውጣት ቁፋሮ ሊጀመር መሆኑን አብራርተውልኛል ብሏል ኢሰመኮ።
ኮሚሽነር ጀነራል የኑስ ሙሉ ለታራሚዎች የሚመደበው በጀት ማስተካከያ እዲደረግላቸው በቅርቡ በተወካዮች ምክር ቤት መጠየቃቸው ይታወሳል፡፡
የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን በስሩ 6 ማረሚያ ቤቶችን ያስተዳድራል፡፡
በቃሊቲ ማረሚያ ማዕከል የነበሩ የ2 ሺህ 200 የሚሆኑ ታራሚዎች በተለምዶ አባ ሳሙኤል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ወደተገነባው አዲስ ማረሚያ ቤት የተዘዋወሩት ባሳለፍነው ታህሳስ ወር ላይ ነበረ፡፡
በኢትዮጵያ በ16 እስር ቤቶች ውስጥ ከ120 ሺህ በላይ እስረኞች እንዳሏት ዓለም አቀፉ የማረሚያ ቤት ለውጥ እና ማገገሚያ ማዕከል የኢትዮጵያ ቢሮ ሪፖርት ያስረዳል፡፡
በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ወቅት ስርጭቱን ለመቀነስ ሲባል ኢትዮጵያ 40 ሺህ እስረኞችን መልቀቋ ይታወሳል፡፡