የአንጎላ ፕሬዝዳንት ዣዎ ሎሬንስ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀ መንበር ሆኑ

አንጎላ የ2025 አፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበርነትን ከሞሪታኒያ በይፋ ተረክባለች።

38ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ዛሬ በሕብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።

በጉባኤው መክፈቻ መርሃ ግብር የወቅቱ የሕብረቱ ሊቀ መንበር ሞሪታኒያ ለአንጎላ ሊቀ መንበርነቷን በይፋ አስረክባለች።

የ2024 የአፍሪካ ሕብረት ሊቀ መንበር የነበሩት የሞሪታኒያ ፕሬዝዳንት መሐመድ ኦውልድ ጋዙዋኒ ለአንጎላ ፕሬዝዳንት ዣዎ ማኑኤል ጎንሳልቬስ ሎሬንስ በ2025 የአፍሪካ ሕብረትን በሊቀ መንበርነት እንዲመሩ አስረክበዋል።

የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር በየዓመቱ በአባል ሀገራቱ የሚመራ ሲሆን በ2025 ዓመት አንጎላ ተረኛ ሊቀመንበር ሀገር ሆና ትቀጥላለች፡፡

ከዛሬ ጀምሮ ለሁት ቀናት የሚመክረው የመሪዎች ጉባዔ ከሁለት ቀናት በፊት በተጠናቀቀው 46ኛው የሕብረቱ የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት በመደበኛ ስብሰባ በተለዩ አጀንዳዎች ላይ ይመክራል።

ከዘንድሮው የመሪዎች ጉባዔ አጀንዳዎች መካከል የሕብረቱ ተቋማዊ ማሻሻያዎች፣ የማካካሻ ፍትህ፣ የአፍሪካ በመንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ ውክልና ጉዳይ እና አህጉራዊ ሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ይገኙበታል።

የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና አፈጻጸምና አህጉራዊ የንግድና ኢኮኖሚ ትስስር፣ግብርናና የአየር ንብረት ለውጥ፣ ሰብዓዊ መብቶች፣ ስርዓተ ጾታና ወጣቶችን ማብቃት እንዲሁም የተቋማትና አደረጃጀቶች ምርጫም የጉባዔው አካል የሆኑ ቁልፍ አጀንዳዎች ናቸው።

የዘንድሮው የአፍሪካ ህብረት በአባል ሀገራት የመሪዎች ጉባኤ ላይ ከዚህ በፊቱ በተሻለ ቁጥር ያላቸው መሪዎች የተገኙበት ሲሆን የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ፣ የናይጀሪያ ፕሬዝዳንት ቲኑቡ፣ የዛምቢያ፣ ቦትስዋና፣ኬንያ፣ ሩዋንዳ እና ሌሎችም ሀገራት ፕሬዝዳንቶች ተገኝተዋል፡፡

By New admin

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *