በካሜሩን አስተናጋጅነት የተካሄደው የመላው አፍሪካ አትሌቲክስ ውድድር ተጠናቋል፡፡
በካሜሩን ዋና ከተማ ዱዋላ አስተናጋጅነት ከ27 ሃገራት በላይ የተውጣጡ 2500 አትሌቶች ላለፉበት 6 ቀናት ሲሳተፉበት የነበረው 23ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ውድድር ተጠናቋል።
በዚህ ውድድር ለይ የተሳተፈው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን አራተኛ ሆኖ አጠናቋል፡፡
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና 5 ወርቅ፣ 4 የብር እና አንድ የነሐስ በድምሩ 10 ሜዳሊያዎችን አግኝቷል፡፡
ኢትዮጵያጵያ በውድድሩ ላይ 68 አትሌቶችን በ19 የአትሌቲክስ የውድድር አይነቶች ላይ የተሳተፈች ሲሆን ከናይጀሪያ በመቀጠል አራተኛ ሆና አጠናቃለች፡፡
የወርቅ ሜዳልያ ለኢትዮጵያ ያስገኙ አትሌቶች ፋንታዬ በላይነህ በ5ሺ ሜትር ሴቶች ፣ንብረት መላክ በ10ሺ ሜትር ወንዶች ፣ምስጋና ዋቁማ በወንዶች በ20 ኪሎ ሜትር እርምጃ፣ ስንታየሁ ማስሬ በሴቶች በ20 ኪሎ ሜትር እርምጃ እንዲሁም ሳሮን በርሄ በ1500 ሜትር ሴቶች አንደኛ ሆነው አጠናቀዋል፡፡
ውብርስት አስቻል በ5ሺ ሜትር ሴቶች፣ገመቹ ዲዳ በ10ሺ ሜትር ወንዶች፣ አለምናት ዋለ በ3ሺ መሠናክል ሴቶች፣ አትሌት ንብረት መላክ በ5ሺ ሜትር ወንዶች ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳልያዎችን አስገኝተዋል።
እንዲሁም አትሌት ገላ ሀምበሴ በ10ሺ ሜትር ሴቶች ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳልያ ለኢትዮጵያ አምጥታለች፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በውድድሩ ላይ ሜዳሊያ ላመጡ አትሌቶች እና አሰልጣኞች የማበረታቻ ገንዘብ ሽልማት አበርክቷል፡፡
ውድድሩን ደቡብ አፍሪካ በ7 ወርቅ፣ በ5 ብር እና 8 ነሀስ በድምሩ 20 ሜዳሊያዎችን በማግኘት በአንደኝነት ስታጠናቅቅ ኬንያ በ5 ወርቅ፣7 ብር እንዲሁም በ7 ነሀስ በድምሩ በ19 ሜዳሊያዎች ሁለተኛ እንዲሁም ናይጀሪያ በ5 ወርቅ፣ 6 ነሀስ እና 4 ነሀስ በድምሩ በ15 ሜዳሊያዎች ሶስተኛ ሆኖ አጠናቋል፡፡