የኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ 1ሺህ 1መቶ ሀኪሞችን ለመቅጠር ባለፈዉ ዓመት ሰኔ ወር 2015 ዓ.ም ማስታወቂያ ቢያወጣም ተቀጣሪዎችን ባለማግኘቱ በጀቱን ወደ ሌላ ዘረፍ ማዛወሩን ለኢትዮ ኤፍ ኤም አስታዉቋል፡፡
የቢሮዉ ምክትል ሃላፊ ዶ/ር ጉሻ በለኮ በሰኔ 2015 ላይ 1ሺህ 1መቶ ሀኪሞችን ለመቅጠር ማስታወቂያ የወጣ ቢሆንም ተቀጣሪዎችን ባለማግኘቱ ቢሮዉ በጀቱን ለሌላ ጉዳይ ማዋሉን ለጣቢያችን ተናግረዋል፡፡
ለ 2 ወራት ያክል ማስታወቂያዉን ክፍት ባደርግም ገበያ ላይ ተቀጣሪዎችን አላገኘሁም ብሏል ቢሮዉ፡፡
በየአንዳንዱ ጤና ተቋም ሀኪሞች መኖር ስላለባቸዉ ያንን ለማሟላት ማስታወቂያ ብናወጣም ሀኪሞችን ባለማግኘታችን በምትኩ የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችን፣ አዋላጆችን እና ነርሶችን ለመቅጠር ተገደናል ነዉ ያሉት፡፡
ከዚህ በፊት ለመላዉ ኦሮሚያ አገልግሎት የሚሰጡ የጤና ባለሙያዎች ቁጥር 72ሺህ ነበር ያሉት ሃላፊዉ አሁን ላይ ቁጥሩ ወደ 85ሺህ ከፍ ማለቱን ነግረዉናል፡፡
በተቻለን አቅም ማስታወቂያ አዉጥተን ገበያ ላይ የነበሩትን ለመዉሰድ ሞክረናል ነገርግን አሁንም የሀኪሞች ዕጥረት አለ ብለዋል፡፡
ማስታወቂያዉን አይተዉ የመጡትን እንቀጥራለን ፤ካልመጡ ግን ገበያዉ ላይ የሰዉ ሃይል እንደሌለ ነዉ የሚቆጠረዉ ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ሃላፊዉ በተጨማሪም ባለፈዉ ዓመት ሃኪሞችን ለመቅጠር ባወጣነዉ ማስታወቂያ ሀኪሞችን ማግኘት ስላልቻልን ወደ 7 መቶ አከባቢ የሚሆኑ የተለያዩ ባለሙያዎችን ቀጥረናል ሲሉም ነግረዉናል፡፡