በጃፓን ካሳማ ከተማ ለአትሌት አበበ ቢቂላ የመታሰቢያ መንገድ ተሰየመ
በጃፓን ካሳማ ከተማ አትሌት አበበ ቢቂላን ለማስታወስ የግማሽ ማራቶን መንገድ በስሙ መሰየሙን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
የስያሜ ስነ-ስርዓቱ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበልን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራን፣ በጃፓን የኢትዮጵያ አምባሳደር ዳባ ደበሌን እና የካሳማ ከተማ ከንቲባን ጨምሮ በርካታ ባለስልጣናት በተገኙበት ተከናውኗል።
በስነ-ስርዓቱ ላይ የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል ይህ የመታሰቢያ ስያሜ ለአትሌቱ ክብር ከመስጠት በተጨማሪ በኢትዮጵያ እና በጃፓን መካከል ያለውን ጥብቅ ወዳጅነት እና የባህል ትስስር የሚያሳይ እንደሆነ ገልጸዋል።
አትሌት አበበ ቢቂላ በ1964ቱ የቶኪዮ ኦሎምፒክ ያገኘው ድል ኢትዮጵያን ያስጠራ ብቻ ሳይሆን በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነትም አጠናክሯል ብለዋል።
በጃፓን የኢትዮጵያ አምባሳደር ደባ ደበሌ በበኩላቸው ጃፓናውያን ይህንን ቀን ለዘመናት እንደሚያስታውሱ እና የአትሌት አበበ ቢቂላ ድል በጃፓን ማህበረሰብ ውስጥ ትልቅ ቦታ እንዳለው መግለጻቸውን ሚኒስቴሩ አስታውቋል።
የካሳማ ከተማ ከንቲባ ሻንጁ ያማጉቺ ይህ የመታሰቢያ መንገድ በሁለቱ አገራት ሕዝቦች መካከል ያለውን ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል።
በኦሎምፒክ ውድድሮች የማራቶን ሯጭ የሆነው አትሌት አበበ ቢቂላ በሮም ኦሎምፒክ አንደኛ በመውጣት ለኢትዮጵያ እና ለጥቁር ህዝቦች የመጀመሪያው አሸናፊ አትሌት ነው።
አትሌት አበበ ከሮም ኦሎምፒክ በተጨማሪም በጃፓን አዘጋጅነት በተካሄደው የቶኪዮ ኦሎምፒክ ላይ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል።