የተለያዩ አገራት በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ኹከትና የዜጎች ሞት እንዳሳሰባቸው ገለጹ
በኢትዮጵያ የአውሮፓ ኅብረት ልዑክን ጨምሮ የተለያዩ አገራት ኤምባሲዎች ሰሞኑን በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ኹከት፣ የዜጎች ሞትና አለመረጋጋት እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል።
የአውሮፓ ኅብረት ልዑክ በኢትዮጵያን እና የኦስትሪያ፣ የቤልጂየም፣ የቼክ ሪፖብሊክ፣ የዴንማርክ ፣ የፊንላንድ፣ የፈረንሳይ፣ የጀርን፣ የሃንጋሪ፣ የአየርላንድ ፣ የኢጣሊያ፣ የሉክሰምበርግ፣ የማልታ፣ የኔዘርላንድስ፣ የሮማኒያ፣ የፖላንድ፣ የፖርቱጋል፣ የስሎቬንያ፣ የስፔን እና የስዊድን ኤምባሲዎች የአማራ ክልል ወቅታዊ ሁኔታን አስመልክተው የጋራ መግለጫ አውጥተዋል፡፡
በመግለጫቸውም በክልሉ የተቀሰቀሰው ኹከት፣ የዜጎች ሞትና አለመረጋጋት እንዳሳሰባቸው የገለጹ ሲሆን፤ ኹሉም ወገኖች ሲቪሎችን እንዲጠብቁ፣ ጉዳት ለደረሰባቸው ህዝቦች የተሟላ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ እና ቀጣይነት ያለው ሰብአዊ ተደራሽነት እንዲረጋገጥ፣ የውጪ ዜጎች ከግጭቱ አካባቢ ለቅቀው እንዲወጡ እና ደህንነቱ በተጠበቀ ኹኔታ እንዲተላለፉ እንዲፈቀድ ጠይቀዋል፡፡
በተጨማሪም የሰላም ስምምነቱ አፈፃፀም በሚቀጥልበት ጊዜ ውስብስብ ጉዳዮችን በሰላማዊ ውይይት ለመፍታት በጋራ መስራት፣ እና ግጭቱ ወደ ሌሎች የአገሪቱ ክልሎች ተዛምቶ ብጥብጥ እንዳይፈጠር ተገቢው መከላከል እንዲደረግም አሳስበዋል፡፡
አለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ለኹሉም ኢትዮጵያውያን የረዥም ጊዜ የረጋጋት ግብ ድጋፉን እንደሚቀጥልም ተገልጿል፡፡