አሜሪካን ጨምሮ የተለያዩ የውጭ ሀገራት ዲፕሎማቶቻቸውን ከሱዳን ካርቱም ማስወጣት ጀምረዋል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን፣ በሱዳን ካርቱም የሚገኙ ዲፕሎማቶች እና ቤተሰቦቻቸው በዛሬው ዕለት ሀገሪቷን ለቀው መውጣታቸውን ተናግረዋል፡፡
ዲፕሎማቶቹ የአሜሪካ ጦር ባካሄደው የተሳካ ኦፕሬሽን ከሱዳን ካርቱም በሰላም መውጣት ችለዋል ተብሏል።
ፕሬዚዳንት ባይደን ዲፕሎማቶችን ለማስወጣት ለተደረገው የተሳካ ስራ ለኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ እና ሳዑዲ ዓረቢያ መንግስታት ምስጋና አቅርበዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ አሁን ላይ በሱዳን የሚገኘው የዩናይትድ ስቴትስ ኤምባሲ አገልግሎት መስጠት እንዳቆመ አረጋግጠዋል።
በተመሳሳይ 150 የሚሆኑ የሳዑዲ ዓረቢያ፣ ግብጽ፣ ካናዳ፣ ሕንድ፣ ኩዌት፣ ፓኪስታን እና የቱኒዚያ ዲፕሎማቶች እና የዓለም አቀፍ ተቋማት አመራሮች በባህር ከሱዳን ሳዑዲ ዓረቢያ መግባታቸው ተገልጿል።
ፈረንሳይ፣ ቻይና፣ ብሪታንያ፣ ስፔን እና ሌሎች ሀገራትም በሱዳን ካርቱም የሚገኙ ዲፕሎማቶቻቸውን ለማስወጣት ስራ መጀመራቸው ተጠቁሟል።
በሱዳን ካርቱም ከዘጠኝ ቀናት በፊት በሱዳን ብሔራዊ ጦር እና በሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ተጀመረው ጦርነት ዛሬም እንደቀጠለ ነው።
ለኢድ አልፈጥር በዓል ተብሎ በመላው ሱዳን የሶስት ቀናት የተኩስ አቁም ስምምነት ቢደረግም ጦርነቱ እንደቀጠለ ነው።
የውጭ ሀገራት በካርቱም ኤርፖርት በኩል ዜጎቻቸውን ለማስወጣት ቢሞክሩም ጦርነቱ በመቀጠሉ ምክንያት በኢትዮጵያ መተማ በኩል በየብስ ትራንስፖርት እያስወጡ ነው ተብላል።