የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ ፕሬዝዳንት ሼክ መሃመድ ቢን ዛይድ አል ናህያን ለይፋዊ የስራ ጉብኝት አዲስ አበባ ገብተዋል።
ሼክ መሃመድ ቢን ዛይድ አል ናህንያን አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) አቀባበል አድርገውላቸዋል።
ፕሬዝዳንቱ በኢትዮጵያ ቆይታቸው ከተለያዩ የመንግስት የስራ ኃፊዎች ጋር ተገናኝተው እንደሚወያዩ ይጠበቃል።
ሼክ መሃመድ ቢን ዛይድ ፕሬዝዳንት ከሆኑ በኋላ በኢትዮጵያ ጉብኝት ሲያደርጉ ይህ የመጀመሪያቸው ሲሆን ከዚህ ቀደም የአቡዳቢ አልጋ ወራሽ በነበሩበት ወቅት በ2018 በኢትዮጵያ ጉብኝት አድርገው ነበር።
ሁለቱ ሀገራት የጠበቀ ወዳጅነት ያላቸው ሀገራት ሲሆኑ በተለይም በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ወደ ዱባይ እና አቡዳቢ በማምራት በመስራት ላይ ናቸው፡፡
እንዲሁም ሁለቱ ሀገራት በሰው ሀብት ልማት፣ በንግድ እና ኢንቨስትመንት፣ በጸጥታ እና ደህንነት ዙሪያ በጋራ በመስራት ላይ ናቸው፡፡
የተባበሩት አረብ ኢምሬት ኢትዮጵያ ላለፉት ሁለት ዓመታት ከህወሃት ጋር በነበረው ጦርነት ወቅት የጦር መሳሪያ፣ የገንዘብ እና ዲፕሎማሲ ድጋፍ በማድረግ ትታወቃለች፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ወደ ስልጣን ከመጡ ጊዜ በኋላ ከአምስት ጊዜ በላይ ወደ አቡዳቢ ተጉዘው ጉብኝት እና ውይይት አድርገው ተመልሰዋል፡፡