ቱርክ የኢትዮጵያ ሁለተኛዋ የንግድ እና ኢንቨስትመንት አጋር ሆነች

የኢትዮጵያና የቱርክ የንግድና የኢንቨስትመንት ግንኙነትን የሚያጠናከር የቢዝነስ ኮንፈረንስ እና ኤግዚቢሽን በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው።

በቱርኩ የአለም አቀፍ የኢንዱስትሪ ትብብር ፎረም/ World Cooperation of Industries Forum-WCI Forum/ / እና በአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት አማካኝነት የተሰናዳው ስምንተኛው የ ደብሊው ሲአይ / WCI የቢዝነስ ፎረም ዛሬ ተጀምሯል፡ ፡

በንግድ ፎረሙ ላይ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር  ዘለቀ ተመስገን፤ የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት/ አዲስ ቻምበር/ ፕሬዚዳንት  ዘሀራ መሀመድ፤ የዲፕሎማቲክ እና የንግዱ ማህበረሰብ እና  ሌሎች ጥሪ ተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል፡ ፡

በመድረኩ ላይ መልእክታቸውን ያስተላለፉት የአዲስ ቻምበር ዋና ፀሀፊ መሰረት ሞላ የኢትዮጵያ እና የቱርክ አመታዊ የንግድ ልውውጥ መጠን እ.አ.አ በ2023 ከ 1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር መብለጡን ተናግረው ሁለቱ ሀገራት ካላቸው እምቅ አቅም አንፃር ከዚህ በላይ መሰራት እንዳላበት ገልፀዋል ፡፡

አዲስ ቻምበርም የሀገራቱን የንግድ ማህበረሰብ በማቀራረብ እና ትስስር በመፍጠር የኢትዮጵያን ንግድና ኢንቨስትመንት መጠንን ማሳደግ እንደሚቻልና ለዚህም አዲስ ቻምበር በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል፡ ፡

በመድረኩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን እንዳሉት ኢትዮጵያ የቱርክ ባለሀብቶች ዋነኛ መዳረሻ መሆንዋን ጠቅሰው አሁንም ካለቸው ታሪካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት እና አቅም አንፃር የቱርክ ባለሀብቶች በሰፊው በየዘርፉ እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ከ2 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሀብት ያላቸው ከ260 በላይ የቱርክ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፍ መሰማራታቸው ተገልጿል።

ይህም ቱርክ ከቻይና በመቀጠል ሁለተኛዋ የኢንቨስትመንት አጋር አድርጓታል።

በቱርክ ኤምባሲ የንግድ ካውንስለር የሆኑት ጣሃ አልፕሬን በበኩላቸው ኢትዮጵያና ቱርክ ረዥም ታሪካዊ ግንኙነት ቢኖራቸውም የንግድ ልውውጣቸውን እና የኢንቨስትመንት መጠናቸውን አሁንም ማሳደግ እንደሚያስፈልግ ጠቁመው የቱርክ ባለሀብቶች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው እንዲያለሙና የኢትዮጵያም አቻዎች በቱርክ ያለውን የገበያ እድል እንዲያማትሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በንግድ ፎረሙ ላይ ከ200 በላይ የአዲስ ቻምበር አባላትና ከ20 በላይ ግዙፍ የቱርክ የንግዱ ማግበረሰብ አባላት ተገኝተው የንግድ ለንግድ ግንኙነት አድርገዋል፡ ፡

የኢትዮ ቱርክ የቢዝነስ ኮንፈረንስ እና ኤግዚቢሽን ለ2 ተከታታይ ቀናት እንደሚቆይ ለማወቅ ተችሏል፡

By New admin

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *