ሚኒስቴሩ በተያዘው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ 649 ቢሊዮን ብር ሰብስቤያለሁ ብሏል
ገቢው ከአምናው ተመሳሳይ ጊዜ 74 በመቶ ወይም የ279 ቢሊየን ብር ብልጫ ያለው ነው ተብሏል፡፡
ከተሰበሰበው ገቢ 345.9 ቢሊየን ብሩ ከታክስ የተገኘ ሲሆን ከወጭ ንግድ ቀረጥና ታክስ ደግሞ 307.2 ቢሊየን ብር መሰብሰቡ ተገልጿል።
ገቢው በመቶ ቢሊዮኖች ከአምናው ከፍ ያለበት ምክንያት ግን በሪፖርቱ አልተብራራም፡፡
በሌላ በኩል ህገ-ወጥ ንግድ ፣ ገቢን መደበቅ ፣ ግብይትን ያለ ደረሰኝ መከወን ፣ ግብር ስወራና ታክስ ማጭበርበር አሁንም ፈተና ሆነውብኛል ብሏል ሚኒስቴሩ፡፡
ተሰውሮብኝ ነበር ያለውን ገቢ ለማግኘትም በድንገተኛ ፍተሻ ፣ በሒሳብ ምርመራ ወይም ኦዲትና መሰል ስራዎች የህግ ማስከበር ስራ ሰርቻለሁ ብሏል፡፡
በዚህም 7 ሺህ 583 የሒሳብ መዝገቦችን ኦዲት አድርጌ ከነወለድና መቀመጫው ከ60 ቢሊዮን ብር በላይ እንዲከፍሉም ተወስኗል ተብሏል፡፡
የታክስ ማጭበርበር ፈፅመዋል የተባሉ 641 ድርጅቶችም ተለይተው ሒሳባቸው ተመርምሯል ያለው ሚኒስቴሩ ከ235 ድርጅቶች የ3.4 ቢሊየን ብር ዋጋ ያላቸው ሐሰተኛ የግዥ ደረሰኞችን ይዣለሁ ሲል በሪፖርቱ አስፍሯል፡፡
በሌላ በኩል 19 ድርጅቶች ከ5 ቢሊየን ብር በላይ ታክስ ሊከፈልበት የሚገባን ገቢ ደብቀው ተገኝተዋልም ተብሏል፡፡
ግብይት ሲፈፅሙ ደረሰኝ ሳይቆርጡ የተያዙ 597 ተጠርጣሪዎችም በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በወንጀል ምርመራና በክስ ሂደት ላይ እንደሆኑ ተገልጿል።
በተጨማሪም በኦዲት ምርመራ የተለያዩ 584 ድርጅቶችን ኦዲት በማድረግ ወለድና መቀጫን ጨምሮ 25.8 ቢሊየን ብር እንዲከፍሉ እንደተወሰነባቸው በሪፖርቱ ላይ ተጠቅሷል፡፡
በአጠቃላይ በመደበኛና በምርመራ ኦዲት በሂሳብ መዝገባቸው ያልተገባ ኪሳራ ካቀረቡ ድርጅቶችም 26.2 ቢሊየን ብር መቀበሉን ፣ ተመላሽ ይደረግልን ብለው ከጠየቁ ደግሞ 2.6 ቢሊየን ብር ማስቀረት ችያለሁ ሲል የገቢዎች ሚኒስቴር ተናግሯል፡፡
ሌላው ሚኒስቴር መ/ቤቱ ፈተና ሆኖብኛል ባለው የኮንትሮባንድ ንግድም ባለፉት 9 ወራት 15.6 ቢሊየን ብር የተገመቱ ገቢና ወጭ የኮንትሮባንድ እቃዎች ተይዘዋል ብሏል፡፡