በአዲስ አበባ የ12ኛ ክፍል ፈተና ተፈታኞች በቡድን መደባደባቸው ተገለጸ
በጎንደር ዩኒቨርስቲ የ12ተኛ ክፍል ፈተና ፈታኝ እና ሁለት ፖሊሶች መገደላቸውን ትምህርት ሚኒስቴር አረጋግጧል
የ12ኛ ክፍል ፈተናን ለመፈተን ከአዲስ አበባ ከተማ ካሉ የመንግስት እና የግል ትምህርት ቤቶች ወደ ዩንቨርሲቲ የመጡ ተማሪዎች በቡድን መደባደባቸውን የትምህርት ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡
ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ላይ እንዳሉት በትምህር ቤቶቻቸው በመቧደን ተደባድበዋል ያሉት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የዶርም በር፣ ሎከር እና ሌሎች አካላዊ ጉዳት ደርሷል ብለዋል፡፡
ፖሊስ ክስተቱን እያጣራ ነው ያሉት ሚኒስትሩ 87 ተማሪዎች ተይዘው ምርመራ በመካሄድ ላይ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለም ከአዲስ አበባ ውጪ በጎንደር እና በጋምቤላ የ12ኛ ክፍል ፈተና በተወሰነ ደረጃ መስተጓጎሉ ተገልጿል፡፡
በጎንደር በተከሰተው ግጭት ምክንያት 16 ሺህ ተፈታኝ ተማሪዎች የአንድ ቀን ከግማሽ ፈተናዎችን ያልወሰዱ ሲሆን አንድ ፈታኝ እና ሁለት የፌደራል ፖሊስ አባላት ተገድለዋል ተብሏል፡፡
በጋምቤላ ደግሞ ከምግብ ጋር በተያያዘ 38 ተማሪዎች በህመም ምክንያት ፈተናውን እንዳልወሰዱ ተገልጿል፡፡
ፈተናውን ያልወሰዱ ተማሪዎች እጣ ፈንታ ምንድን ነው ያልናቸው ሚኒስት በቀጣይ ፈተናውን የሚወስዱበትን መንገድ እናመቻቻለን ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በአጠቃላይ በዘንድሮው ፈተና 840 ሺህ 859 ተማሪዎች የ12ኛ ክፍል ፈተናን መፈተናቸውን ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በመግለጫቸው ላይ ገልጸዋል፡፡