ብሔራዊ ባንክ የዶላር ጨረታ በየ15 ቀኑ በተከታታይ አወጣለሁም ብሏል
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በየሁለት ሳምንት መደበኛ የውጭ ምንዛሪ ሽያጭ ጨረታ ማካሄድ እንደሚጀምር አስታወቀ።
ጨረታዎቹ ለሚቀጥሉት በርካታ ወራት የሚካሄዱ ሲሆን፣ ዓላማውም የማዕከላዊ ባንኩን የተረጋጋ የውጭ ምንዛሬ ስርዓት ግብን ለማሳካት ነው ብሏል።
የማዕከላዊ ባንኩ የውጭ ምንዛሪ መጠባበቂያ ክምችት በታሪኩ ከፍተኛው እንደሆነ ገልጾ በተለይ ከቅርብ ወራት ወዲህ፣ በሀገሪቱ ውስጥ ብቸኛው የወርቅ ገዥ ለሆነው ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የቀረበው የወርቅ መጠን ከፍተኛ መሆን የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪ መጠባበቂያ ክምችት ከተገመተው በላይ እንዲጨምር እንዳደረገው ጠቁሟል።
ከዚህ ከተጠበቀው በላይ ከሆነው የውጭ ምንዛሪ ግኝት አንጻር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በቀጣይ ወራት በመደበኛነት በየሁለት ሳምንቱ የውጭ ምንዛሪ ሽያጭ ጨረታዎችን ለማካሄድ መወሰኑን አሳውቋል።
ይህ አካሄድ በማዕካላዊ ባንክ እየተከማቸ ካለው የውጭ ምንዛሪ የተወሰነውን መጠን ለግሉ ዘርፍ ለማቅረብና የማዕከላዊ ባንኩን የገንዘብ ፖሊሲ ዓላማ ለማሳካት የሚረዳ እንደሆነ አመልክቷል።
ፍላጎቱ ያላቸው ባንኮች በተሰጠው የጊዜ ሰሌዳና በተቀመጠው አኳኌን የጨረታ ስነዶቻቸውን እንዲያስገቡ ባንኩ ጥሪ አድርጓል።
ብሔራዊ ባንክ ከአንድ ወር በፊት የ60 ሚሊዮን ዶላር ጨረታ ያወጣ ሲሆን ሶስት ባንኮች አንድ የአሜሪካ ዶላርን በ135 ብር ለመግዛት ማሸነፋቸው ይታወሳል፡፡