ሐገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከክልሎች የምክክር አጀንዳ ሊያሰባስብ መሆኑን አስታወቀ

ኮሚሽኑ በክልሎች የሚያደርገውን የሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የማሰባሰብ ስራ በመጪው ሳምንት እንደሚጀምር አስታውቋል።

አጀንዳ የማሰባሰብ ስራው ድሬዳዋ ከተማ አሰተዳደርን ጨምሮ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በጋምቤላ እና በሀረሪ ክልሎች እንደሚካሄድም ነው ያስታወቀው ኮሚሽኑ።

ሂደቱን በማስመልከት መግለጫ የሰጡት የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ኮሚሽነር አቶ ዘገየ አስፋው አጀንዳ በማሰባሰብ ስራው የሚሳተፉ ተወካዮች መረጣ አስቀድሞ በመጠናቀቁ ስራው ድሬዳዋን ጨምሮ በሶስቱ ክልሎች ይካሄዳል ብለዋል።

ከሳምንት በኋላ ቀደም ሲል በተጠቀሱት ሶስት ክልሎች ይካሄዳል የተባለው አጀንዳ የማሰባሰብ ስራ ከአዲስ አበባው ጋር ተመሳሳይ በሆነ ሂደት እንደሚፈጸምም ነው ኮሚሽነር ዘገየ የተናገሩት።

በየክልሉ ካሉ 10 የህብረተሰብ ክፍሎች የተመረጡ የወረዳ ተወካዮች ወደ ክልል ከተሞቹ እንዲመጡ ከተደረገ በኋላ ተመካክረው አጀንዳዎቻቸውን እንዲለዩና ከክልል ባለድርሻ አካላት ጋር እንዲመካከሩ ይደረጋል ብለዋል።

“ከወረዳዎች ተወክለው የመጡት የህብረተሰብ ክፍሎች፤ በክልሉ ላይ ካሉ ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ በመሆን የየክልሉን አጀንዳዎች” እንደሚለዩና

“በዋናው ሀገራዊ ጉባኤ የሚወክሏቸውን ተወካዮች” እንደሚመርጡም ነው ኮሚሽነር ዘገየ ያስረዱት።

ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ከአሁን ቀደም ማለትም ባሳለፍነው ወርሀ ግንቦት መጨረሻ በአዲስ አበባ አጀንዳዎችን ማሰባሰቡ የሚታወስ ነው።

By New admin

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *