በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ያጋጠመውን የጸጥታ ችግር ተከትሎ የመሰረታዊ ምግብ አቅርቦቶች እጥረት አጋጥሟል፤፡
የምርት እጥረት ማጋጠሙን ተከትሎም ህዝቡ በዋጋ ንረት እየተጎዳ እንደሆበነም ተገልጿል፡፡
የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ በከተማዋ ያጋጠመውን የሽንኩርት እጥረት ለመፍታት ከሱዳን ለማምጣት ማቀዱን አስታውቋል፡፡
ከበዓላቱ ጋር ተያይዞ የሽንኩርት ዋጋ ጭማሪ በማሳየቱ እና በየጊዜው በአትክልት ላይ ለሚደረገው የዋጋ ጭማሪ መፍትሄ ተብለው እየተሰሩ ያሉ ስራዎች መኖራቸውን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ አስታውቋል።
የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ እንደተናገሩት በመደበኛ ገበያው ላይ ለተከሰተው የዋጋ ንረት መፍትሄ ተብለው እየተሰሩ ያሉ ስራዎች መኖራቸውን ተናግረዋል፡፡
በተለይ የእሁድ ገበያ ላይ ከሸማች ህብረት ስራ ማህበራት ጋር በተያያዘ እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ መሆኑን እና ሱዳንን ጨምሮ ከተለያዩ ሀገራት ሽንኩርት ወደ ከተማዋ ለማስገባት ጥረት እየተደረገ እንደሆነ አንስተዋል።
ቢሮው ሽንኩርትን ከውጪ ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት እና ለሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ድጋፍ ለማድረግ እስከ 1.4 ቢሊየን ብር በጀት መመደቡ ተገልጿል፡፡
በአትክልት ዋጋ ላይ የተፈጠረው የዋጋ ጭማሪ እንደ ምክንያት ብለው ያነሱት ያለው አቅርቦት ከፍላጎቱ ጋር ባለመጣጣሙ እና በህገወጥ ንግድ ምክንያት መሆኑን ጠቁመዋል።
በአዲስ አበባ ባሳለፈነው ሳምንት አንድ ኪሎ ሽንኩርት እስከ 120 ብር ድረስ ሲሸጥ የነበረ ሲሆን አሁን ላይ ከ70-100 ብር በመሸጥ ላይ ይገኛል፡፡
በኢትዮጵያ በተለይም በኦሮሚያ፣ አማራ እና ትግራይ ክልሎች ያለው የጸጥታ ችግሮች የዜጎችን ህይወት እየጎዱ ሲሆን የኑሮ ውድነቱንም እያባባሱት ይገኛሉ፡፡
ከዚህ በተጨማሪም የፌደራል መንግስት ስንዴ በስፋት የማምረት እቅድ መያዙ ከዚህ በፊት አትክልት እና ፍራፍሬ ይመረትባቸው የነበሩ አካባቢዎች ተገደው ስንዴ እንዲያመርቱ መደረጉ ለምርት እጥረቱ ሌላኛው ምክንያት ነው ተብሏል፡፡