በኢትዮጵያ የቴሌግራም መተግበሪያ የማህበራዊ ትስስር ገጽ ከዛሬ ረቡዕ ሐምሌ 19 ቀን 2015ዓ.ም ጠዋት ጀምሮ እየሰራ አይደለም።
ገደቡ የተጣለዉ ዛሬ ከሚጀመረዉ የ 2015 ዓ.ም የ 12ኛ ክፍል ፈተና ጋር በተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል።
ይሁንና መንግሥት ለምን በቴሌግራም ላይ እገዳ እንደጣለ እስካሁን መረጃ ያልሰጠ ሲሆን መተግበሪያው በቪፒኤን እየሰራ ይገኛል።
ከወራት በፊት በኦሮሚያ ክልል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አጋጥሟት የነበረዉን የመከፋፈል ድርጊትና የጳጳሳት ሹመነትን በሚመለከት በተለያዩ አካባቢዎች የተነሳዉን ተቋዉሞ ተከትሎ በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ እግዱ ተጥሎ ለአምስት ወራት መቆየቱ ይታወሳል።
በዚህም መሰረት እንደ ፌስቡክ ፣ ቲክቶክ ፣ ቴሌግራም ፣ ኢንስታግራም ፣ ዩቲዩብ እና ሌሎች የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎችን ሰዎች VPN ( virtual private network ) ቪፒኤንን በመጠቀም ሲገለገሉ ቆይተዋል።
ኢትዮጵያ ለአምስት ወራት በተወሰኑ የማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ እገዳ በመጣሏ ስምንት ቢሊዮን ብር ገቢ ማጣቷን ኔት ብሎክስ የተሰኘው የቴክኖሎጂ ተቋም አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንን ጨምሮ በርካታ የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ተቋማት መንግሥት በኢንተርኔት ላይ የጣለውን ገደብ እንዲያነሳ ሲያሳስቡ ቆይተዋል።