በሱዳን መከላከያና በፈጥኖ ደራሽ ሐይል መካከል በካርቱምእና አካባቢው የተነሳው ጦርነት በከተማዋ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንን ችግር ላይ እንደጣላቸው ተገልጿል።
በስፍራው የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን እንደነገሩን ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ችግር ላይ ናቸው።
ኢትዮጵያዊያን በግለሰቦች ቤት ተጠልለው እንደሚገኙም የተገለጸ ሲሆን በተኩስ ልውውጡ የሞቱ እና የቆሰሉ መኖራቸውንም ሰምተናል።
በጀነራል አቡድልፋታህ አልቡርሃን የሚመራው የሰዱን ጦር እና በጀነራል ሀምዳን ዳጋሎ ወይም ሄመቲ ሀይሎች መካከል ይፋዊ ጦርነት ሲካሄድ ዛሬ ሶስተኛ ቀኑ ላይ ይገኛል።
እስካሁን በዘለቀው ጦርነት ከ100 በላይ ንጹሀን ሲገደሉ ከ600 በላይ ዜጎች ደግሞ ቆስለዋል ተብሏል።
አሜሪካ፣ አውሮፓ ህብረት፣ ሩሲያ፣ ሳውዲ አረቢያ እና በርካታ የዓለማችን ሀገራት ተፋላሚ ወገኖች ጦርነት እንዲያቆሙ በማሳሰብ ላይ ናቸው።
በካርቱም ያለው የኢትዮጵያ ኢምባሲ ዜጎች ከቤት እንዳይወጡ እና ራሳቸውን ከግጭት እንዲያርቁ አሳስቧል።
ለሁለት ተከፍሎ እየተዋጋ ያለው የሱዳን የጸጥታ ሀይሎች አንዳቸው በአንዳቸው ላይ ድል መቀዳጀታቸውን እየተናገሩ ይገኛሉ።
ኤርፖርቶችን፣ ወታደራዊ ማዘዣዎችን እና ቤተ መንግስቱን ለመቆጣጠር ጦርነቱ የቀጠለ ሲሆን የተኩስ አቁም እንዲደረግ ፈቃደኞችም እንዳልኮኑ ተገልጿል።